ታረቀኝ ዘነበ
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የግንባታ ሥራን ለማስቆም በግብጽ መንግስት ፖለቲከኞች፣ ምሁራንና መገናኛ ብዙሃን መሣሪያነት የዋሉት በርካቶች ቢሆኑም፤ “ድሆች ናቸው” ከሚለው እስከ ማስፈራሪያ ዛቻዎች ድረስ ጥቅም ላይ እንዲውሉ ማድረጋቸው የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡
በግብፅ በተከሰተው ፖለቲካዊ ቀውስ ሳቢያ ከሙባረክ እስከ
ሙርሲ ብሎም እስከ አሁኑ በፊልድ ማርሻል አል-ሲሲ የሚዘወረው ጊዜያዊ መንግስት ድረስ በርካታ ገዥዎች በትረ
ስልጣኑን ቢቆናጠጡም፤ በዓባይ ውኃ ላይ የሚያራምዱት አስተሳሰብ ግን ልዩነት የተስተዋለበት አይመስለኝም፡፡
ይልቁንም የፖለቲካ አስተሳሰባቸውን ወደ ጎን በማድረግ የዓባይ ጉዳይ የህዝባቸው የመኖርና ያለመኖር ጉዳይ እንደሆነ ያለ ልዩነት ሲናገሩ እየተደመጡ ዛሬ ላይ መድረሳቸውን አስረጅ የሚያስፈልገው አይመስለኝም—ሲከውኑት የነበሩት ተግባሮቻቸው አፍ አውጥተው ይናገራሉና። ለህዝባቸው ጥቅም መረጋገጥም ሽንጣቸውን ገትረው መከራከሩን ብሔራዊ አጀንዳቸው አድርገው መቀጠላቸውም እንዲሁ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የሀገራችንን የህዳሴ ጉዞ የማሳካት፣ ሀገራዊውን የፀረ - ድህነት ትግል ከዳር የማድረስ ከፍተኛ ድርሻ ያለውና ከድህነት መውጫ መሰላል የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለመላው ኢትዮጵያዊ የህይወት ጉዳይ መሆኑ ለድርድር የማይቀርብ ቢሆንም፤ በሀገራችን ፖለቲከኞች፣ ምሁራንና መገናኛ ብዙሃን በኩል ብሔራዊ አጀንዳ አድርጎ ከመንቀሳቀስ አኳያ ግን ውጤታማ መሆኑን ለመናገር የሚያስደፍር አይመስለኝም፡፡