Tuesday, 29 December 2015

እኛና ታላቁ የህዳሴ ግድብ

ታረቀኝ ዘነበ  
 
    
       
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የግንባታ ሥራን ለማስቆም በግብጽ መንግስት ፖለቲከኞች፣ ምሁራንና መገናኛ ብዙሃን መሣሪያነት የዋሉት በርካቶች ቢሆኑም፤ “ድሆች ናቸው” ከሚለው እስከ ማስፈራሪያ ዛቻዎች ድረስ ጥቅም ላይ እንዲውሉ ማድረጋቸው የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡ 
በግብፅ በተከሰተው ፖለቲካዊ ቀውስ ሳቢያ ከሙባረክ እስከ ሙርሲ ብሎም እስከ አሁኑ በፊልድ ማርሻል አል-ሲሲ የሚዘወረው ጊዜያዊ መንግስት ድረስ በርካታ ገዥዎች በትረ ስልጣኑን ቢቆናጠጡም፤ በዓባይ ውኃ ላይ የሚያራምዱት አስተሳሰብ ግን ልዩነት የተስተዋለበት አይመስለኝም፡፡ 

ይልቁንም የፖለቲካ አስተሳሰባቸውን ወደ ጎን በማድረግ የዓባይ ጉዳይ የህዝባቸው የመኖርና ያለመኖር ጉዳይ እንደሆነ ያለ ልዩነት ሲናገሩ እየተደመጡ ዛሬ ላይ መድረሳቸውን አስረጅ የሚያስፈልገው አይመስለኝም—ሲከውኑት የነበሩት ተግባሮቻቸው አፍ አውጥተው ይናገራሉና። ለህዝባቸው ጥቅም መረጋገጥም ሽንጣቸውን ገትረው መከራከሩን ብሔራዊ አጀንዳቸው አድርገው መቀጠላቸውም እንዲሁ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የሀገራችንን የህዳሴ ጉዞ የማሳካት፣ ሀገራዊውን የፀረ - ድህነት ትግል ከዳር የማድረስ ከፍተኛ ድርሻ ያለውና ከድህነት መውጫ መሰላል የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለመላው ኢትዮጵያዊ የህይወት ጉዳይ መሆኑ ለድርድር የማይቀርብ ቢሆንም፤ በሀገራችን ፖለቲከኞች፣ ምሁራንና መገናኛ ብዙሃን በኩል ብሔራዊ አጀንዳ አድርጎ ከመንቀሳቀስ አኳያ ግን ውጤታማ መሆኑን ለመናገር የሚያስደፍር አይመስለኝም፡፡ 

Sunday, 27 December 2015

ከሁከቱ ምን አተረፍን ?




ዮናስ
መነሻውን የአዲስ አበባባና በዙሪያዋ የሚገኙ ከተሞችን የተቀናጀ ፕላን በማድረግ በአንዳንድ የኦሮሚያ ከተሞች በተማሪዎች የተጀመረው ተቃውሞ በተወሰኑ አካባቢዎች መልኩን እየቀየረ ወደ ሁከት በመምራቱ መንግስት አስፈላጊውን እርምጃ እየወሰደ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ይህንኑ ተከትሎ ታዲያ ስለሃገራችን ጸጥታ ደንታ የሌላቸውና ይልቁንም አበረታች እንደሆኑ የሚታወቁቱ ሁሉ የመግለጫ ጋጋታውን ተያይዘውታል፡፡


መንግሥት በኦሮሚያ የተነሳውን መጠነ ሰፊ ተቃውሞ ለማርገብ ያልተመጣጠነ ኃይል ከመጠቀም እንዲቆጠብ በማለት ያሳሰበውና የለመድነው ደግሞ አምነስቲ የተሰኘው ነው፡፡
አምነስቲ ኢንተርናሽናልና ሂውማን ራይትስ ዎች ሰሞኑን በጉዳዩ ላይ ባወጡት መግለጫ፤ መንግስት ተቃውሞ በሚያሰሙ አካላት ላይ ያልተመጣጠነ ኃይል ከመጠቀም እንዲቆጠብ ጠይቀዋል፡፡ መንግሥት የዜጎችን ሃሳብን በነፃነት የመግለፅና ሰላማዊ ተቃውሞ የማድረግ መብት ከማክበር ይልቅ ጉዳዩን ከሽብርተኝነት ጋር ማያያዙ አግባብ አይደለም ብሏል አምነስቲ፡፡ የነዚሁ ድርጅቶች አጃቢ እና አራጋቢው መድረክ ደግሞ እንዲህ አለ፡፡
ተቃውሞውን ተከትሎ በተፈጠረው ግጭት 32 ሰዎች በመንግስት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን ያስታወቀ ሲሆን አምነስቲ ኢንተርናሽናል የሟቾች ቁጥር ወደ 40 እንደሚጠጋ ገልጿል። የሙሾው ተቀባይ ደግሞመንግሥት ተቃውሞ ያሰሙትን ሁሉ በሽብርተኝነት ፈርጇል ከህግ አግባብ ውጪ በፀጥታ ኃይሎች የሚፈፀምን ግድያ ከማውገዝ ይልቅ ተቃዋሚዎቹን ሽብርተኛና ሀገር ሊበጠብጡ የተነሱ ናቸው ማለቱ አግባብ አይደለም ሲል ተቃውሟል። የውዝግቡ መነሻ ከሆነው ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ 2006 . ተመሳሳይ ግጭት ተፈጥሮ የበርካቶች ህይወት ጠፍቶ እንደነበር ያስታወሰው ሂውማን ራይትስ ዎች በበኩሉ፤ ያኔም ሆነ አሁን በተነሳው ተቃውሞ በርካቶች መገደላቸውን፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ መታሰራቸውን አስታውቋል፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት በተነሳው ተቃውሞ አብዛኞቹ የተቃውሞው ተሳታፊዎች ተቃውሞ ስላቀረቡ ብቻ ጉዳዩ ከሽብር ተቆጥሮ በሽብር እንደተፈረደባቸው የጠቀሰው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ በወቅቱ ታስረው የነበሩ ተማሪዎች በእስር ቤት ውስጥ ግርፋትና ስቃይ ደርሶባቸዋል ብሏል፡፡ ከሦስት ሳምንታት በላይ ለዘለቀው ተቃውሞ መንግሥት የፀጥታ ኃይሎቹ ከመጠን በላይ ኃይል እንዳይጠቀሙ ሊከላከል ይገባ ነበር ያለው "የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ" ህግ የጣሱ አካላት በገለልተኛ ወገን ተጣርቶ ተገቢውን ቅጣት ማግኘት አለባቸው ብሏል፡፡